ኢትዮጵያ የምዘና ስርአትን በሀገርና በአፍሪካ እንዲስፋፋ ከአፍሪካና ከኢትዮጵያና የምዘና ማህበራት ጋር በጋራ ለመስራት የተጀመረውን ስራ አጠናክራ እንደምትቀጥል የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዶ/ር ፍጹም አሰፋ ገለፁ።
==========================================================================
አዲስ አበባ | ሰኔ 9/2017
ክብርት ሚኒስትሯ ይህንን የገለፁት ዛሬ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ተከብሮ በዋለው 25ኛ ዓመት የአፍሪካ የምዘና ማህበር የምስረታ በአል መክፈቻ ላይ ነው። ዶ/ር ፍጹም በእለቱ እንደተናገሩት የአፍሪካና የምዘና ማህበር ላለፉት ሩብ ምዕተ-አመታት በአህጉሪቱ ግምገማን በማስተዋወቅ ረገድ የልህቀት ምልክት ሆኖ ቆይቷል፡፡
25ኛው የምስረታ በአል በኢትዮጵያ መከበሩ በምሳሌነቱና ብቻ ሳይሆን በጣም ተገቢ እንደሆነ የገለፁት ዶ/ር ፍጹም አዲስ አበባ የአፍሪካ አንድነት ማዕከል መሆኗን ፣ የፖሊሲ የሃሳብ ንግግሮች እና የተቋማት እድገትን ማሳያ ጭምር ነው ብለዋል። በዚሁ መሰረት የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የምዘና ስርአት እንዲሰፋፋ ከአፍሪካና ከኢትዮጵያና የምዘና ማህበራት ጋር በቅርበት ለመስራት የተጀመረውን ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል፡፡
ዶ/ር ፍጹም ፕላንና ልማት ሚኒስቴር በፌዴራል የመንግስት ተቋማት ላይ ተጨባጭ የምዘና ርምጃ እያካሄደ መሆኑን ጠቁመው የሀገር አቀፍ የግምገማ ፖሊሲ ማዕቀፍ በማዘጋጀትና በመተግበር፤ በአስር አመት መሪ የልማት እቅድ የምዘና ስርአትን በማካተት ፤ የህዝብ ኢንቨስትመንቶች ወቅታዊ እና ጥብቅ ምዘናዎች የሚደረግባቸው መሆኑና የ‹‹አንድ ዕቅድ አንድ ሪፖርት›› ሥርዓትን ማስተዋወቅ መቻሉና የክትትልና ግምገማ ስርዓታትን ዲጅታላይዜሽን ማድረግ በምዘና ሂደት በሀገሪቱ ከተከናወኑ ቁልፍ ስኬቶች ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡